Followers

Friday, January 30, 2026

ኖሮ ኖሮ ከሞት፤ ዞሮ ዞሮ አዙሪት በአብራሃም ለቤዛ

 


ኖሮ ኖሮ ከሞት፤ ዞሮ ዞሮ አዙሪት

በአብራሃም ለቤዛ

የሜሮን ጌትነትን ግጥም እያዳመጥኩ የፃፍኩት

------------------////----------------------

ያ ስዩም መስፍን  ባድሜ ተሰጠን ፤

የጦር ሜዳ ድሉን በአደባባይ ደገምን፤

ውጣና ተደሰት ዘምባባውን ይዘህ ፤

ተሸከርክና ጨፍር ፈንዲሻህን ደፍተህ፤

የሚል ሳክስ ነበር በቲቪው የነፋው፤

ዲጂታል ሳይበዛ ካድሬና ወረፋው፤

ይኸን ሳንረሳው በዚያኛው ዘመን፤

እነቶኔ ሆነው ከወያኔ ነፃ አውጭ፤

ተረታቸው ሆነ በረጂሙ ትግል ስላደሩት ውጭ፤

ጦርነት አውርደው ደም እንዳላፈሱ፤

በአንዴ እጥፍ ብለው ጲላጦስን ሆነው፤

እኛ መቼ ለኳስን ነው ግፋ በለው ናቸው ብለው አላከኩ ፤

ሰው እንዳለለቀ በነሱ ዳፋ ጦስ፤

እስክስ፤

ይኸው ታረቅን ኢትዮጵያ አሸነፈች፤

አራት ኪሎም አለች፤

ማንም ሳይጠየቅ የሞተ ተጎዳ፤

እንዲሆን ተረቱ የሀገሬው ፍዳ፤

ፕሪቶሪያ ሄደው ፤ሃላላ ተዝናንተው፤

ውስኪ እየተራጩ  አንሶላ ተጋፈው፤

ዛሬም ተመልሰው ይኸው አየናቸው ፤

ከአዙሪቱ ወድቀው፤

 

Thursday, July 24, 2025

አድማሱ “ዛፍ” በቆረጠበት ጊዜ - (የዩኒቨርሲቲው ሥነ ውበታዊ ክስመት) [ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ]

 


“እና – እንደኔና እንዳንቺው የውበት ዐይኑ የታወረ፣
እግረ ኅሊናው የከረረ፤
ባሕረ ሐሳቡን ያልታደለ፣
የውበት ዐይኑ የሰለለ፣
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ አበባ እኮ አይደለም አለ፡፡
ያልታደለ፤…” (“እሳት ወይ አበባ”)

መግቢያ
ታኅሣሥ 29 ቀን፣ 2009 ዓ.ም. በዓለ ገና፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ዕድገትና ደረጃን በሚመለከት በጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን ትምህርት ቤት በሚያስተምር ግለሰብ ዋና የመረጃ ሰጪነት፣ ዘጋቢ ፕሮግራም በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ተላልፎ ነበር፤ የፕሮግራሙ አቀራረብም፣ የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬን ማዕከል ያደረገ ነበር፡፡ እንዲኽ ዓይነት ይዘት ያለውን የዶክመንተሪ አቀራረብ፣ አሜሪካኖች* “Charm offensive” ይሉታል፡፡

ይህን ሲሉ፣ ኾን ተብሎና ታቅዶ፣ የራስን የማንነት ውበትና በጎነት አጉልቶ በማውጣት የሚቀርብ ድርጊትን መግለጻቸው ነው፡፡ ይህንኑ የራስ መልክአ ውዳሴ ወደ አማርኛ ስንተረጉመው፣ “አጀብ እዩልኝ” ተብሎ ሊገለጽ ይችላል፡፡ ዶክመንተሪው በዋናነት፣ የዩኒቨርሲቲውን ጉዳይ ያነሣ ቢመስልም፣ ዐቢይ ትኩረቱ ግን፣ ፕሬዝዳንቱን እንዲኹም የሥራ አፈጻጸማቸውን አጉልቶ ለማውጣት ያለመ ነው፡፡ ኾኖም፣ እውነታው* በመልክአ ውዳሴው ከቀረበው የዩኒቨርሲቲው ኹኔታ እንዲኹም፣ ከፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ ገጸ ሰብእና ጋር ሲነጻጸር ፈጽሞ የተራራቀ ነው፡፡

ይህን ጽሑፍ እንዳዘጋጅ የወዲያው ሰበብ የኾነኝ፣ ይህንኑ የእውነታ መራራቅና መጣረስ ለማሳየት በማሰብ ነው፡፡ ኹለተኛውና ዋነኛው የጽሑፌ መንሥኤ ግን፤ በፕሬዝዳንት አድማሱ እና በቦርዱ ሊቀ መንበር አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን ይኹንታ ሰጪነት፣ በዩኒቨርሲቲው ቅጽር የተካሔደው የዛፍ ምንጠራ ድርጊትና የሕንፃ ግንባታ አስከትሎት ጉዳይ ነው፡፡
ይህ መጣጥፍ፣ የኹለት ክፍሎችን ቅንብር የያዘ ነው፡፡ አንደኛው* የዩኒቨርሲቲውን ዛፍ ምንጠራ እና የዕውቅ ሥነ ውበታዊ መገለጫውን መገፈፍ በየአንጻሩ ማሳየት ሲኾን፤ ኹለተኛው ደግሞ፣ ዛፍ ምንጠራው፣ የዩኒቨርሲቲውን መካነ አእምሯዊ ተልእኮ ለማሳካት ሳይኾን፣ የፕሬዝዳንቱንና ፈቃድ የሰጡትን ሹመኞች ፍላጎትና ጥቅም ታሳቢ ያደረገ ፕሮጀክት መኾኑን በጥቂቱ ማሳየት ነው፡፡

ኢንዱስትሪ እና ዩኒቨርስቲ

የማኅበራዊ ሳይንስ ተመራማሪውና በኢትዮጵያ ጉዳዮች በርካታ ጥናቶችን ያሳተሙት ፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን፣ ከኅልፈታቸው ጥቂት ዓመታት ቀደም ብለው* “Powers of the Mind: The Renovation of Liberal Learning in America” በሚል ርእስ፣ ስለ ዩኒቨርሲቲ ፍልስፍና መጽሐፍ አሳትመው ነበር፡፡ ፕሮፌሰር ሌቪን፣ ስለ ዩኒቨርሲቲ ምንነት በርካታ ጥልቅ ሐሳቦችን የገለጹ ቢኾንም፤ ከዚኽ መጣጥፍ ዋና ይዘትና መንፈስ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለውን አንዱን አገላለጻቸውን ብቻ ወስደናል፡፡

ፕሮፌሰር ሌቪን፣ “ዩኒቨርሲቲ፣ በኢንዱስትሪ የውጤታማነት መለኪያ መስፈርት ሊመዘን አይገባም፤” ይላሉ፡፡ እንደ እርሳቸው አገላለጽ፣ ዩኒቨርሲቲ በኢንዱስትሪ መለኪያ የማይመዘንበት ምክንያት* በይዘት፣ በዓላማም ኾነ በውጤት ከኢንዱስትሪ የተለየ በመኾኑ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር፣ ዩኒቨርሲቲ እንደ ኢንዱስትሪ ገበያ የሚፈልገውን ብቻ ፈብርኮ የሚያቀርብ ሳይኾን፣ ተማሪዎች፣ ለጥናትና ምርምር የተኮተኮተ አእምሯዊ ማሕቀፍ እንዲኖራቸው ለማስቻል የተደበረ የዕውቀት ኀሠሣ ማዕከል በመኾኑ ነው፡፡

ይህን መሠረታዊ የዩኒቨርሲቲ እና የኢንዱስትሪ ባሕርያዊ ልዩነት በውል ባለመገንዘብ፤ የወቅቱ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ፤ መድረክ ባገኙባቸው አጋጣሚዎችና ከላይ በጠቀስነው “የአጀብ እዩልኝ” ዶክመንተሪያቸው ሳይቀር፤ ስለሚመሩት ዩኒቨርሲቲ ሲገልጹ፣ ደጋግመው የሚጠቀሙባቸው ዕዝሎችና ቅጽሎች፡- ‹አደረጃጀት›፣ ‹ሽፋን›፣ ‹ቅበላ›፣ ‹ቁጥር›፣ ‹ግንባታ›፣ ‹የኃይል ትስስር›፣ ‹ፕሮጀክት›፣ ‹አንድ ለአምስት› … ወዘተ. ናቸው፡፡

ከላይ የተዘረዘሩት ቅጽሎችና ሐረጎች፤ የኢንዱስትሪ የምርታማነትና የውጤት ደረጃ አመልካች መለኪያዎች፤ የአንድ ፋብሪካ የምርት ቁጥጥር ሓላፊ ወይም የሕንፃ ግንባታ ተቆጣጣሪ “ካቦ”፣ በሚያቀርበው ሪፖርት የሚጠቀማቸው ቃላት እንጂ፣ “ⷈሉ አመክሩ ወዘሠናየ አጽንዑ”(ኹሉን መርምሩ መልካሙንም አጽንታችኹ ያዙ) የሚለውን ታላቅ ኃይለ ቃል ይዞ የተነሣን፣ የማእምራን መዲና የኾነ ዩኒቨርሲቲን መንፈስ የሚወክል ወይም የሚመጥን አይደለም፡፡

“አድማሱ ዛፍ የመነጠረበት ዘመን”

የዚኽን ንኡስ ርእስ ሐሳብ የወሰድኹት፣ በጎጃም ጠቅላይ ግዛት ታዋቂ ከኾነና በስፋት ከሚነገር ታሪክ ወስዶ፣ አንድ ወዳጄ በአንድ ወቅት ያጫወተኝን ትረካ መሠረት አድርጌ ነው፡፡ ትረካው በአጭሩ ሲቀርብ እንደሚከተለው ነው፡፡

ልዑል ራስ ኃይሉ እና ዐፄ ኃይለ ሥላሴ፣ በራስ ካሳ ሥር ታስረው በነበሩት በልጅ ኢያሱ ከእስር ቤት ማምለጥ፤ ራስ ኃይሉ፣ “ተሻርከው አስመልጠዋል” በሚል ምክንያት የከረረ ጠብ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ልዑል ራስ ኃይሉም ከጎጃም አገረ ገዥነት ተሽረው በእስርና በግዞት ይሰደዳሉ፡፡ በምትካቸውም፣ ከንቲባ ማተቤ ደረሶ ደብረ ማርቆስን ተሾሙ፡፡ ይህን የሥልጣን ሽግግር አገሬው ስላልወደደው፣ የራስ ኃይሉን ልጅ ፊታውራሪ አድማሱ ኃይሉን ይዞ ተቃውሞ ቀሰቀሰ። በጊዜውም በደብረ ማርቆስ ቤተ መንግሥት ግምጃ ቤት ውስጥ በግብር የተሰበሰበና የራስ ኃይሉም የግል ንብረት የነበረ ሀብት፤ “የሸዋ ሹመኞች መጥተው ሊወስዱት ነው፤” ተብሎ ስለተወራ፤ እነፊታውራሪ አድማሱ፤ “ይህ ንብረት ሸዋ ከሚሻገር ጎጃሜ ይውሰደው!” በማለት፤ ግምጃ ቤቱን ከፍተው በሕዝብ አስመዘበሩት፡፡ ይህም ድርጊት እስከ ዛሬ በጎጃም፣ “አድማሱ ያፈረሰው ጊዜ” ተብሎ ሲወሳ ይኖራል፡፡

ወደ ጥንተ ነገራችን ስንመለስ፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት አድማሱ ጸጋዬ፣ “ለዩኒቨርሲቲው ማስፋፊያ ሕንፃ መገንባት አስፈላጊ ነው፤” በሚል መነሻ፣ የቅጽረ ግቢው ግርማ ሞገስ ኾኖ በዓለም የሚታወቀውን ዐጸድ በማስመንጠር፣ የማይበጅ አፍራሽ ተግባር ፈጽመዋል፡፡
የኹለቱም “አድማሱ”ዎች ድርጊት፣ በጥቅሉ “የአፍራሽ” ቅጽል ተሰጥቶት ቢገለጽም፤ የመጀመሪያው አድማሱ የተነሡበት መንፈስ፣ ለጎጃም ሕዝብ ወገንተኝነት የቆመ ሲኾን፤ ይህም ድርጊታቸው በጊዜው በሕግ ቢያስጠይቃቸውም፣ ከሞራል አንጻር ሲታይ ግን የሚያስኰንናቸው ጉዳይ አይደለም፡፡ የኹለተኛው አድማሱ አፍራሽነት ግን፤ በሕግም ኾነ በሞራል መስፈርት ያስጠይቃቸዋል፡፡ ይኸውም፣ ከዩኒቨርሲቲው ቅጽር ሥነ ውበት አንጻር የሚያስጠይቅ ስሕተት ተፈጽሟል፤ የሚል እምነት ስላለኝ ነው፡፡

የመጀመሪያው አድማሱ አፍራሽነት፣ ስሕተት ከተባለ መግፍኤው፣ ለሕዝብ ከመቆም ሲኾን፤ የኹለተኛው አድማሱ የአፍራሽነት ድርጊት ግላዊና መለካዊ (ሥልጣን ሰገድ) ከመኾን የመነጨ ነው፤ ማለት እንችላለን። በመኾኑም፣ የቀዳሚው አድማሱ ድርጊት፣ አንድ ማኅበረሰባዊ ተረክ ኾኖ እንደቆየን ኹሉ፣ የዩኒቨርስቲው አድማሱ የደን ምንጣሮ አፍራሽነትም ለትውልድ ሲነገር ይኖራል፡፡

የደን ምንጣሮው፡- ከሥነ ሕይወት፣ ከሥነ ውበት እና ከፎክሎር አተያዮች አንጻር፤

ሀ/ሥነ ሕይወት
የዛፍን ምንነትና ኹለንተናዊ ጥቅም አስመልክተው፣ ወ/ሮ ዕሌኒ መኩሪያ የተባሉ ዕውቅ ጋዜጠኛ፤ “ዛፎች ለሕይወት” በሚል ርእስ በ2005 ዓ.ም. መጽሐፍ አዘጋጅተው ነበር፡፡ በመጽሐፉ ውስጥ ስለ ዛፍ እና ሥነ ሕይወት* ማብራሪያዎች፣ ፎቶግራፎች፣ ግጥሞችና መጣጥፎች ተካተውበታል፡፡ የእኒኽ ዓይነት መጻሕፍት ዓላማ፤ ዛፍ እንዳይመነጠርና ለዛፍ ክብካቤ እንዲደረግ አበክሮ ማሳሰብ በመኾኑ፤ ስለ ሥነ ሕይወት እና ሥነ ምኅዳር ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ኾኖ አግኝቼዋለኹ። ይህን በመሰለ ጥረት፣ ለማኅበረሰቡ የዛፍን ጥቅም በወል ለማስጨበጥና ለማስተማር በሚሞከርበት ጊዜ፤ ዩኒቨርሲቲው፣ ሲኾን፣ ከነወ/ሮ ዕሌኒ መኩሪያ ጋር በአስተማሪነት ይሰለፋል ብለን ስናስብ፤ በተቃራኒው የዛፍ ጭፍጨፋ ተግባር ላይ ተሰልፎ መገኘቱ ብዙዎችን አሳዝኗል፡፡

የወቅቱ የዩኒቨርሲቲው አመራር እና አስተዳደር፣ ዩኒቨርሲቲው ለመጪው ትውልድ የሚያገለግል ዐጸድ መትከልና አኹን ያሉትንም መከባከብ ሲገባው፤ ራሱ ያልተከለውንና ከዘመናት በፊት የነበረውን ደን መመንጠሩ፣ ዩኒቨርሲቲው፣ ስለ አካባቢ ጥበቃ አስፈላጊነት ለማኅበረሰቡ ለማስተማር የነበረውን የዕውቀትና የሞራል ልዕልና እንዲያጣ ምክንያት ኾኗል፡፡
እንዲኽ ያለው ብዝኃ ሕይወትን የመጠበቅና የመከባከብ ሓላፊነት፤ እንደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያለው ተቋም ይቅርና በዜግነት ደረጃ እንኳን ግለሰብ ሊፈጽመው እንደሚገባ፤ በአንድ ወቅት ደጃዝማች ዘውዴ ገብረ ሥላሴ፣ የደን ምንጠራን በመቃወም ካሳዩት አርኣያነት የምንረዳው ነው፡፡

ከጥቂት ዐሥርት ዓመታት በፊት፣ በፈረንሳይ ለጋሲዮንና በቤላ መካከል በሚገኝ በአንድ በደን በተሸፈነ ይዞታ ላይ ምንጣሮ ሊካሔድ አስተዳደራዊ ውሳኔ ተላልፎ ነበር፡፡ በተጠቀሰው አካባቢ ያለው ደን፣ ከአዲስ አበባ ምሥረታ ኹለትና ሦስት ምእተ ዓመታት ቀድሞ የነበረና ሀገር በቀል ዕፀዋትን የያዘ ነው፡፡ ደጃዝማች ዘውዴ፣ በእነዚኽ ዕፀዋት ላይ የተላለፈው የምንጣሮ ውሳኔ እጅግ የተሳሳተ መኾኑን ለመግለጽ፣ የአካባቢውን ማኅበረሰብ አስተባብረው ተቃውሟቸውን በማቅረብ ምንጣሮውን ማስቀረት መቻላቸው ይነገርላቸዋል፡፡

ከደጃዝማቹ አርኣያነት ያለው ዜግነታዊ ተግባርና እነወ/ሮ ዕሌኒ ካሳተሙት የደን ኹኔታን ከሚያሳይ መጽሐፍ መንፈስ፣ በብዙ መልኩ፣ ለተፈጥሮ በተለይም ለደን ክብካቤ መቆም እንደሚገባን እንረዳለን፡፡ በአንጻሩ፣ የዩኒቨርሲቲው ድርጊት አሳዛኝ ከመኾን አልፎ መንግሥታዊ ይኹንታ ላለማግኘቱ ማረጋገጫ የለንም። በመኾኑም፣ ስሕተቱ፣ የዩኒቨርሲቲው አመራር ብቻ ሳይኾን፣ መንግሥትን ወክሎ የተቀመጠው የቦርዱም ሓላፊነት ያለበት ጭምር እንደኾነ ልብ ይሏል፡፡

ለ/ሥነ ውበት
አንድ ሰው* ስለ ጥበብ፣ ስለ ተፈጥሮ፣ ስለ ውበት… ወዘተ. መረዳት የሚችለው፣ ለተፈጥሮ የሚማልል ንቁና ሥሡ ስሜት ሲኖረው ነው፡፡ ይህ ስሜት ደግሞ፣ በተፈጥሮ የሚገኝ ብቻ ሳይኾን፣ ከትምህርት እና ከአድናቆት ጋር በተያያዘ ስሜታችን ሲኮተኮትና ሲሠለጥን የሚገኝ ነው፡፡ ግለሰቡ ውስጣዊ ጉጉት ካለው በእነዚኽ ጉዳዮች ይደነቃል፤ ይደመማል፤ ይማረካል፤ ይማራል፤ ይቆረቆራል፡፡ ነገር ግን፣ ግለሰቡ፣ የሥነ ውበት መማረክ ከሌለው፣ ውስጡ በሥነ ውበት ስእነት(ኢከሃሊነት) የተሞላ ሕጹጽ ነው፤ ማለት ነው፡፡

ይህን ለመግለጽ፣ አንዳንድ ሠዓሊዎች ግድግዳ ላይ የተሰቀለን ሥነ ጥበባዊ ሥራ አይተው፣ “ከፊል ቦታ ላይ ‘dead spot’ ስላለው መስተካከል አለበት” የሚል ሞያዊ አገላለጽ ይጠቀማሉ፤ ቀለም አንሶታል፤ ሕይወት አልባ ነው፤ ለዛ የለውም፤ ደብዝዟል፤… ወዘተ. ማለታቸው ነው፡፡ ይህን ብሂል ወደ ሰው ስናመጣው፣ ግለሰቡ ወይም ግለሰቧ፣ ሥነ ውበትን ለማድነቅ የሚያስችላቸው የስሜት ሕዋሳቸው በድኗል ወይም አልተኮተኮተም ማለት ነው፡፡ በመኾኑም፣ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንትና ይኹንታ የሰጡት የቦርድ ሹመኞች፤ ከሥነ ውበት ክሂል አንጻር ርምጃቸውን ስናየው፣ የሥነ ውበት አድናቆት ስእነት(ኢከሃሊነት) ሰለባ መኾናቸውን በግልጽ እንረዳለን።

ታላቁ ባለቅኔና ጸሐፌ ተውኔት ጸጋዬ ገብረ መድኅን፣ በ“እሳት ወይ አበባ” ግጥሙ ላይ፣ ስለ ክሂለ ቢስነት (dead spot) ከተቀኘው ጥቂት ስንኞችን እንጥቀስ፤
“እና – እንደኔና እንዳንቺው የውበት ዐይኑ የታወረ፣
እግረ ኅሊናው የከረረ፤
ባሕረ ሐሳቡን ያልታደለ፣
የውበት ዐይኑ የሰለለ፣
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ አበባ እኮ አይደለም አለ፡፡
ያልታደለ፤…”

በመኾኑም፣ በዩኒቨርሲቲው ግቢ ውስጥ የነበረው ተፈጥሮ የለገሰን ውበት በሚገፈፍ ጊዜ፣ ምን ዓይነት ኹኔታ ይፈጠራል? ብሎ መጠየቁ ተገቢ ነው፡፡ ይህን የሥነ ውበት ረድኤት በተመለከተ፣ ኹለት ፈላስፎች ተጠቃሽ አስተምህሯቸውን በሚከተለው መልኩ አስቀምጠውልን አልፈዋል፡፡

የመጀመሪያው፣ የ18ኛው መ/ክ/ዘ ፈላስፋ ኢማኑኤል ካንት፣ በወሳኝ የሥነ ውበት ድርሳኑ (Critique of Judgment)፣ ሥነ ውበትን በመሠረቱ ሲተረጉመው* “Purposiveness without a purpose” ይለዋል፡፡ ይህም ማለት፣ “ይህ ነው” ተብሎ በግኡዛዊ መስፈርት የማይለካ ኾኖ ግብ ያለው እንደ ማለት ነው፡፡ በእርሱ አገላለጽ፡- ተዝናኖት፣ አማሕልሎት እና ሥነ ውበት ያለው ተፈጥሮም ኾነ ጥበብ፣ ከውስጡ ቀጥተኛ የኾነ የተሰፈረ ዓላማ፣ አመክንዮ ወይም ጥቅም የተቀመጠለት አይደለም። ይልቁንም፤ ውብ የኾነ ነገር ማለት፤ ከውስጡ ምንም ቀጥተኛ ጥቅም ሳናገኘበት፣ በውበቱ ብቻ የምንወደው ወይም የምናደንቀው፤ የረቂቁ ሰብአዊ ተፈጥሯችን የሥነ ውበት አድናቆት ስሕበትና “ረኃብ” በሚፈጥርብን ልዩ ፍላጎት ብቻ የምንወደው ማለት ነው፡፡

ይህን ካንታዊ የሥነ ውበት ገለጻ፤ በሀገራችን ነባር አስተምህሮ ለማንጸር ብንሞክር፣ በቤተ ክህነት የሥነ ፍጥረት ትምህርት ያለውን አጠይቆ እንደ አብነት መጥቀስ እንችላለን፡፡ እንደ አስተምህሮው፣ አዝማደ ፍጥረታት በየወገናቸው ስለ ሦስት ምክንያት (ረብሕ) ተፈጥረዋል፡፡ እኒኽም፣ አንደኛው* ለአንክሮ (ለመደመም)፣ ኹለተኛው* ለተዘክሮ (ለተምህሮ)፤ ሦስተኛው* ለምግበ ሥጋ ወነፍስ ናቸው፡፡

ኢማኑኤል ካንት፣ “ቀጥተኛ የተሰፈረ ጥቅም የሌለው ግን ረብ ያለው፤” የሚለውን አገላለጹን፤ ጥንታዊው የቤተ ክህነት አስተምህሮ፣ “ምክንያተ አንክሮ” ይለዋል፡፡ እግዚአብሔር ዓለምን የፈጠረው፣ ጥቂቱን ለጥቅመ ሥጋ ወነፍስ ሲኾን፤ ብዙውን ግን ለአድናቆት፣ ለመደመም፣ “ወይ የአምላክ ሥራ!” ብለን በአንክሮ የመለኮትን ምስጢር እንድናስተውል፣ የመንፈስ ተመስጦና የልቡና ሐሤት እንድናገኝበት ነው፡፡ ይህን ተሰጥሞ ልቡና እና መንፈሰ ሐሤት የቤተ ክህነቱ አስተምህሮ፥ “አንክሮ” ይለዋል፡፡

ይህን የኢትዮጵያ ጥንታዊ አስተምህሮ እና የኢማኑኤል ካንት “የአንክሮ እና የተደሞ” መሠረተ ሐሳብ፤ ከዛሬው የአዲስ አበባው ዩኒቨርሲቲ የአድማሱ ጸጋዬ አስተዳደር መጠበቅ የዋህነት መኾኑን፣ በዛፍ ምንጠራ – ተማስሎ – ድርጊት ፍንትው ብሎ ታይቷል፤ አስተዳደራዊ አስተሳሰቡ፣ ሥነ ፍጥረት፣ ከጥቅመ ሥጋ ያለፈ ረብሕ እንደሌለው በማያሻማ ኹኔታ አሳይቷልና፡፡

ፍሬድሪክ ሺለር የተባለው የ19ኛው መ/ክ/ዘመን የሥነ ጥበብ ሰው፣ “Letters on the Aesthetic Education of Man” በሚል ርእስ በጻፈው ጦማር፣ ስለ ሥነ ውበት ምንነት በእጅጉ አስደማሚ የኾነ አጭር ጽሑፍ አቅርቧል፡፡ ጽሑፉ፣ በርከት ያሉ ርእሰ ጉዳዮችን ቢያነሣም፣ ከፍጥረት የሚገኝ ውበት ሰውን ሊያጎናጽፍ ስለሚችለው ሐሤት እንደሚከተለው አትቷል፤

ሺለር እንደሚለው፣ የግለሰቡም ኾነ የማኅበረቡ ልዩነት፣ ሥነ ውበት ፊት ሲቀርብ፣ ልዩነቱ ኹሉ ይቀርና በመስሕቡ ተማርኮ ኹሉም፣ እያንዳንዱም ያለ ልዩነት እኩል ለሥነ ውበት ይማልላል፡፡
ይህን የሺለር ሐሳብ ይዘን፣ ዩኒቨርሲቲውን በምናይበት ጊዜ፣ ትላንት ዛፉ ሳይቆረጥ፣ ማንኛችንንም ሊያግባቡን ያልቻሉ* የብሔር፣ የፖለቲካ፣ የሃይማኖት፣ የጾታ፣ የመደብ… ወዘተ. አመለካከቶች ሳያግዱን፤ በግቢው ውስጥ የነበረውን መስሕብ ያለው ዐጸድ ያለ ልዩነት በአንድነት እናደንቅ ነበር፡፡ በአኹኑ ወቅት ግን፣ ይህ ዐጸድ ተጨፍጭፎ በፎቆች ሲተካ፣ ሺለር እንዳለው፣ ከተፈጥሮ ውበት ይገኝ የነበረው ንጽረታዊ አንድነት ተጓድሎ፣ ኹላችንም የጋራ አጽድቆት በማንሰጠው ፎቅ ተተክቷል፡፡

እዚኽ ላይ፣ አስተውሎት እንዲኖረን ይገባል ብዬ የማስበው፣ አገዛዙ፣ የጋራ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ዕሴቶችን የመናድ ባሕርያዊ መገለጫው፤ በቅጽሩም ላይ፣ እንደተለመደው፣ ዜጎች ወደ ግቢው ሲዘልቁ የሚያገኙትን ተፈጥሯዊ የጋራ ደስታ በማውደም እንድንለያይ የማድረግ ተግባሩን እንደተያያዘው እንገነዘባለን፡፡

ሐ/ ፎክሎር
የሰው እና የሥነ ሕይወት መስተጋብር፣ በቅርቡ ከምዕራቡ ዓለም የተዋስነው ወይም በሰበካ የተቀበልነው ጉዳይ ሳይኾን፣ ከጥንት ጀምሮ በተለያዩ የአገራችን ማኅበረሰብ ባህል ውስጥ የነበረ አስተሳሰብና ልማድ ነው፡፡ በአገራችን ማኅበረሰቦች ነባር ባህል ውስጥ፣ ስለ ዛፍ ያለው እሳቤ የተለያየ ቢኾንም፣ በአብዛኛው ዛፍ በሰው ልጅ ሕይወት ያለው አገልግሎት ሥሉጥ እንደኾነ እንረዳለን፡፡

ከአገልግሎቱም መካከል፣ ዛፍ፡- መሰብሰቢያ፣ እርስ በርስ መመካከርያ፣ መጠለያ፣ ዕርቅና አፈርሳታ ማካሔጃ ከመኾኑም በላይ፣ የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ በመኾን ያገለግላል፡፡ ዛፍ፣ በአንዳንድ ማኅበረሰብ ባህል ውስጥ የማንነት ትእምርት ሲኾን፣ ዛፍን ከሕይወት መሠረት ጋራ በማያያዝ፣ የራሳቸውን ጥንተ አመጣጥ በሐተታ – ተፈጥሯዊ – ሚት መልክ የሚያቀርቡ ማኅበረሰቦች በአገራችን እንዳሉ፤ ሰሎሞን ተሾመ፣ “ፎክሎር፤ ምንነቱ እና የጥናቱ የትኩረት አቅጣጫ” በሚለው መጽሐፉ ገልጿል፡፡

በተጨማሪም፣ “ዛፍ የሌለው ደብር* ጽሕም የሌለው መምህር” እንዲሉ፣ አብያተ ክርስቲያናትን በርቀት እይታ የምንለያቸው፣ በዙሪያቸውና በግቢያቸው በከበቧቸው ታላላቅ ዐጸዶች ትእምርታዊነት ነው፡፡ ገዳም ማለትም፣ በአንድ ገጹ* ዱር፣ ጫካ፣ የአራዊት መናኸርያ እንደማለት ነው፡፡(ኪዳነ ወልደ ክፍሌ፣ 302)

ማጠቃለያ
ሰው ምሉእነትን የሚጎናጸፈው፣ ለቁመተ ሥጋው የሚያስፈልገውን ምግብ ስላገኘ ብቻ አይደለም፡፡ ታላቁ መጽሐፍ እንደሚለውም፣ “የሰው ልጅ በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡፡” ይልቁንም፣ ከፍጥረታት ኹሉ የሚለየው የአእምሮ እና የመንፈስ ምግብ ጥያቄው ትልቅ ቦታ ይይዛል፡፡ የአንድ ዩኒቨርሲቲ ተቀዳሚ ሚና፣ ይህንኑ፣ የሰው ልጅ በተፈጥሮ ለማወቅ በብርቱ የሚሻውን አእምሯዊና መንፈሳዊ “መፍቅድ” ለማሟላት መጣር ነው፡፡

ከላይ የጠቀስናቸው ፕ/ር ዶናልድ ሌቪን፣ “በአንዳንድ ዩኒቨርስቲዎች ውስጥ በኅብረ ሠናይ (Common Good) እና በጥቅም – ተኮር – ሠናይ (Utilitarian Good) መካከል ውጥረት ይኖራል፤” ይላሉ፡፡ በእነኚኽ ተፃራሪም ተደጋጋፊም ውጥረቶች መካከል፣ አንድ ዩኒቨርሲቲ በጎ መልክ ይዞ ሊወጣ የሚችለው፣ የጋራ ሠናይ ፍላጎትን፣ ከጥቅም ተኮር ፖሊሲ በላይ በማስቀደም ሲጓዝ ነው። ይህ ሲኾን ግን፣ ጥቅም ተኮር ሠናይነትን አምዘግዝጎ ይጥለዋል ማለት ሳይኾን፤ ይኸው ጥቅም ተኮርነት በጋራው ሠናይ ፍላጎት ውስጥ ተካብቶ የሚቀመጥ በመኾኑ ነው። በአንጻሩ፣ ጥቅም ተኮር ሠናይ፣ የጋራ ሠናይ ፍላጎትን በምልአት ይዞ አይገኝም፡፡
ፕሬዝዳንት አድማሱ፣ የዩኒቨርሲቲውን ልዕልና እና አካዳሚያዊ ንጽሕ (Chastiti) በማስደፈር፣ መንግሥት* “ዕድገት እና ልማት” የሚለውን ፖሊሲ ለማንሰራፋት በሙሉ ልብ ስለ ተሰማሩ፣ በቅጽሩ ውስጥ ያሉት ዐጸዶች ተቆርጠው፣ “ልማት” ለሚባለው ጣዖት ሰለባ እንዲኾኑ አድርገዋል፡፡ ከአእምሯዊ ይልቅ አካላዊ መስፋፋትን አብልጦ አትኩሮት መስጠት፣ የትምህርት ፈላስፎች እንደሚሉት፣ በ“ዳይናሶራዊ ሲንድረም” መለከፍ ነው፡፡

ይኸውም፣ ዳይናሶር፣ ስዒረ ፍጥረት የደረሰበት አካላዊ ግዘፉ እየፋፋ፣ አእምሯዊ ኃይሉ እያጸጸ ቆይቶ፣ ራሱን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ወደማይችልበት ክስመት ደርሶ ህልውናው በመጥፋቱ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም፣ ከምሥረታው አንስቶ የካበተ ምሁራዊ ጥሪትና የታላላቅ ልሂቃን እርሾ ባይኖረው ኖሮ፣ እንደ ፕሬዝዳንት አድማሱ ተግባር፣ የዳይናሶር ሲንድረም ሰለባ ይኾን ነበር፡፡

በተጨማሪም፣ ዩኒቨርሲቲው የተፈደቀለትን በጀት ሙሉ በሙሉ ባለመጠቀም፣ በየዓመቱ በርካታ ሚሊዮን ብሮችን ተመላሽ እንደሚያደርግ የታወቀ ነው፡፡ ይህም ኾኖ እያለ፣ ለዩኒቨርሲቲው ተጨማሪ ገቢ እየተባለ በፕሬዝዳንቱ ቢሮ ፕሮጀክት ተቀርጾ* ከበሬ ማድለብ እስከ ዕንቁላል መሸጥ፤ አልፎም የሱፐር ማርኬት የንግድ ሱቆች የማቋቋሙን ተግባር ተያይዞታል፡፡ እዚኽ ላይ ልብ ልንለው የሚገባን፣ የገንዘብ እጥረት በሌለበት ኹኔታና የተፈደቀለትንም በጀት በአግባቡ ሳይጠቀም፣ ተጨማሪ ገንዘብ ያስፈልገኛል በሚል ሰበብ፣ ከዕውቀት ጋር ባልተያያዙ ንግዶች ላይ መሰማራቱ በብዙ መልኩ ስሕተት ነው፡፡

ዩኒቨርሲቲው ኹሌም ሊተጋበት የሚገባው፣ ነገር ግን፣ ኹሌም በምልአት የማያሳካው ዋናው የአእምሮ ጥሪትንና ጠፍታን ማካበትና ማረጋገጥ ኾኖ ሳለ፣ ባላገደደው ንግዳዊ ተልእኮ ውስጥ መሰማራቱ አስገራሚ ነው፡፡ ምናልባት፣ የመጀመሪያ ተልእኮውን (የአእምሮ ሥልጥንና) ካሟላ በኋላ ወደ ንግድ ቢገባ፣ ችግር አይኖረውም ይኾናል፡፡

በርግጥ ዩኒቨርሲቲው፣ ከሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች ጋራ እንደ ዩኒቨርሲቲ ሲለካ፣ ደረጃው እያሽቆለቆለ መምጣቱ ከማንም ያልተደበቀ እውነታ ቢኾንም፤ የግቢው “ግርማ ሞገሳዊ” የውጭ ገጽታ ግን፣ ኹሌም የሚደነቅና በተለያዩ ሀገራት ጎብኚዎች ጭምር የተመሰከረለት ነበር፡፡ ይህን ግርማ ሞገሱን፣ ዛሬ በፕሬዝዳንት አድማሱ ተነጥቆ ዕርቃኑን ቆሟል፡፡

የዛፉ ምንጣሮ፣ ለዩኒቨርስቲው አካላዊ መስፋፋት አማራጭ የሌለው አመክንዮ ተደርጎ በእነ ፕሬዝዳንት አድማሱ ጥቅም ተኮር አስተሳሰብ ይገለጽ ይኾናል፡፡ ከኹሉ በፊት፣ “አማራጭ የለሽ” ይሉት ይኸው ህወሓታዊ ሜታፊዝክስ(የእኛ ሐሳብ* ትክክለኛው እና ብቸኛው ነው፤ የሚል የሐሳብ ሞኖፖሊ)፣ በተለያዩ አጀንዳዎች እንዳየነው፣ አስቀድሞ የተቆረጠንና የተፈጠመን ነገር፣ ያለተገዳዳሪ ሐሳብ ለማስፈጸም የሚጠቀሙት ዘይቤ ነው፤ ፕሬዝዳንቱም፣ የዚኹ፣ “አማራጭ የለም፤” ባይ የሥርዓቱ ፍልስፍና ሰባኪና አስፈጻሚ ኾነው እናገኛቸዋለን፡፡ በአንጻሩ፣ ዩኒቨርሲቲው፣ እንደ መካነ አእምሮ፣ የአማራጭ የለሽ ፍልስፍናን ሽሮ፣ ለተለያዩ ፕሮብሌሞች ኊልቊ መሳፍርት የሌላቸው አማራጮችን የማቅረብ ሓላፊነት አለበት፡፡ ዩኒቨርሲቲው ለሚፈልገው የማስፋፊያ ሥራ ሌሎች የቦታ አማራጮችን መጠየቅ ሲችል፤ ሥነ ውበትን ገርስሶ፣ የኮንስትራክሽን ጣቢያና የፎቆች ጫካ የመሰለ ትዕይንት መፍጠር ተገቢ አይደለም፡፡

የደን ምንጣሮውንና የሕንፃ ማስፋፊያውን፣ ከፕሬዝዳንቱና ከበላይ ሹሞቻቸው ሕጸጽ አኳያ በየአንጻሩ ለማሳየት ሞክረናል፡፡ በዚኽ ጉዳይ ላይ፣ የዩኒቨርሲቲው ግድፈት የሚያሳየው፣ የ“ኤፒስቲሚክ” እና የ“ኤስቴቲክ” ችግርን ብቻ ሳይኾን፤ የአንድ ቢሊዮን ብር ፕሮጀክትን በ‘ካፒቴንነት’ ለማስተዳደር ከመሻት የመነጨ እንደኾነ መገመት አያስቸግርም፡፡ መቼም፣ ዜጎች ብቻ ሳይኾኑ፣ “ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል” እንዲሉ፣ የአማሳኞቹ ቡድን በስም ዝርዝር ባይነገረንም፣ ስለ ሙስናው መንሰራፋት አንዳንድ የሥርዐቱ ሹመኞችም ቢኾኑ በይፋ ያመኑበት ጉዳይ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሙስና ዕንብርት ተብለው የተለዩና ብዙዎችን ካስማሙት ቀዳሚዎቹ፡- የመሬት አስተዳደር፣ የመንገድና የሕንፃ ግንባታ፣ የገቢዎች እና ጉምሩክ አሠራር ላይ የሚታየው ምዝበራ ነው፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም፣ የአንድ ቢሊዮን ብር በጀት በተያዘለት የግንባታ ፕሮጀክት ውስጥ ሲገባ፤ በተለይ ኦዲት ተደርጎ የማያውቅ ተቋም ከመኾኑ የተነሳ፣ ምንም ዓይነት የሙስና እንቅስቃሴ በፕሮጀክቱ ላይ አይካሔድም ብሎ ማመን ተላላነት ነው፡፡
ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት አጠያያቂ በኾነበት በአኹኑ ጊዜ፤ በየትኛውም ተቋም ስላለው ሙስና ሐቁን መናገር በጣም ያስቸግራል፤ ለዚኽም ነው፣ ልዑል ራስ ካሳ ኃይሉ፣ “ፍኖተ አእምሮ” በተሰኘው መጽሐፋቸው፡- “ነጻነትን ተከባከቧት፤ እውነት ራሷን ትጠብቃለች” ያሉት፡፡ ነጻነት በሀገራችን ገና የተደላደለ ቦታ ስላላገኘች፣ ለጊዜው እውነት ሸሸግ ብላ ለመቀመጥ ስለምትገደድ፣ እኛም፣ ስለ ሙስና ከዚኽ በላይ ለማተት ኹኔታው እንደማይፈቅድልን በመረዳት፣ የያዝነውን በልባችን እንደያዝን ሐሳባችንን በዚኹ እናሳርፋለን፡፡

Wednesday, September 11, 2024

የኢትዮጵያ ወራት እና ስያሜያቸው…!!!(ዳዊት ከበደ ወየሳ)

የኢትዮጵያ ወራት እና ስያሜያቸው…!!!

(ዳዊት ከበደ ወየሳ)

 

በኢትዮጵያ የወራት ስሞች ከጥንት ጀምሮ የነበሩ፤ እርስ በርስ የተወራረሱ ናቸው። አማርኛ ደግሞ በኢትዮጵያውያን ዘንድ እየተስፋፋ የመጣ ቋንቋ እንደመሆኑ መጠን፤ ቃላቶችን ከግዕዝ፣ ከኦሮምኛ፣ ከአፋር፣ ከአረብኛ፣ ከጣልያንኛ እና ካመቸው ወይም ህዝብ የተቀበለውን የራሱ እያደረገ እና እያደገ የመጣ ቋንቋ ነው። ከመስከረም እስከ ጳጉሜ ያሉትን የወራት ስያሜዎች ከመረመርን ደግሞ፤ የዚህን እውነት እንረዳለን…!
ወደ ኢትዮጵያ የወራት ስያሜዎች እና አመጣጣቸው ከመሄዳችን በፊት ግን፤ በአገራችን ካሉት ቋንቋዎች መካከል በኦሮምኛም፤ ተመሳሳይ በሆነ መልኩ የወራት ስሞች በተለያዩ ቦታዎች የተለያየ ስያሜ እንደነበራቸው ማስታወስ እንወዳለን። እነዚህን ልዩ ልዩ ስያሜዎች ወደ አንድ መደበኛ ቃል ማምጣት በማስፈለጉ፤ በኦሮምኛ በተለያዩ ቦታዎች ያሉትን የወራት ስያሜዎች አንድ ላይ ሰብሰብ በማድረግ፤ የተሻለውንና በብዙዎች ዘንድ ጥቅም ላይ የዋለውን ቃል በመምረጥ፤ አሁን በመደበኛ የኦሮምኛ ቃል ውስጥ እንዲካተት ተደርጓል።
ለምሳሌ – የመስከረም ወር “ፉልባና” ይባላል። ስያሜውን ያገኘው ከሜጫ ኦሮሞ ነው። የጥቅምት ወር አንኮሌሳ ይባላል – ከአርሲ እና የባሌ ኦሮሞ የተወሰደ ነው። ህዳር ሶስተኛ ወር ሲሆን አርሲ እና ባሌ ሰደሳ ወይም ሶስተኛ ይሉታል። ቃሉም ከዚያ የመጣ ነው። የታህሳስ ወር በቱለማ ኦሮሞዎች ዘንድ ሙዴ ይባላል። የጥር ወር አማጄ ማለት ሲሆን ስያሜውን ከአርሲ እና ከባሌ ኦሮሞ ነው ያገኘው። ጉራንላ ከቦረና ኦሮሞ የተወሰደ ሲሆን፤ የካቲት ወር ማለት ነው። መጋቢት ወር ቢቶሴሳ ይባላል፤ ስያሜውን ከአርሲና ባሌ ነው ያገኘው። የሚያዝያ ወር ኤልባ የሚባል ሲሆን፤ ከቱለማ ኦሮሞ የተወሰደ ቃል ነው። ከግንቦት ወር ጀምሮ ያሉት ወራት፤ በአርሲ በባሌ፣ በቦረና፣ በጉጂ በቱለማ ተመሳሳይ ትርጉም ስላላቸው ያለምንም ምርጫ ግንቦት – ጫምሳ፤ ሰኔ – ዋጣባጂ፤ ሃምሌ – አዶሌሳ፤ የነሃሴ ወር ደግሞ ሃጋያ ይባላል።
ይህን ያህል የኦሮምኛን ወራት የቃል አመጣጥ ካወቅን ይበቃናል። ነገር ግን እዚህ ላይ የብሄሮችን ቋንቋ ተወራራሽነት ለማሳየት እንድንችል፤ በሲዳማ እና በኦሮምኛ ውስጥ የሚገኙ ወራት መኖራቸውን እናስታውሳቹህ። ለምሳሌ ሳደሳ፣ አርፋሳ፣ አንኮሌሳ፣ አዶሌሳ… የመሳሰሉት የወራት ስሞች በሲዳማ እና በኦሮምኛ ውስጥ በተመሳሳይ ሁኔታ ይገኛሉ። አሁን ደግሞ ከኢትዮጵያ ኩሼቲክ ወደ ሴማዊ ኢትዮጵያ በመሄድ፤ የአማርኛ ወራት ስያሜ ታሪካዊ አመጣጣቸውን ወይም ስለ ስነ-ውልደታቸው እንጨዋወታለን።
መስከረም – የመስከረም ወር አበቦች በየመስኩ የሚፈነዱበት፤ አደይ አበባ ምድሪቱን የሚያለብስበት ወር ነው። ኢትዮጵያውያን ከአገራቸው ውጪ፤ እጅግ ውብ የሆነ አገር ሲባል የሚሰሙት፤ ስለ ሮም እና ሮማውያን ነው። እናም ይህን በአበባ ያጌጠ መስክ – መስከ-ሮም ብለው ይጠሩታል። ይህን ለማረጋገጥ በተመሳሳይ መልኩ ረዥም እድሜ ያለውን የጉራጌ ሴማዊ ቋንቋ ማየቱ ይበቃል። በአብዛኛው የጉራጊኛ ቋንቋ መስከረምን…. መስከሮም ወይም መስከሮብ ይሉታል። አማርኛው ታዲያ ቃሉን ከርክሞ እና አስተካክሎ – መስከረም ብሎ ሰይሞታል።
ጥቅምት – በተለይ በገበሬው ዘንድ የጥቅምት ወር የሚታወቀው፤ ጥራጥሬ ተዘርቶ እሸት የሚያፈራበት ወር በመሆኑ ነው። ይህ ወር ከሌላው ወር በበለጠ፤ ለገበሬው እና ለከብቶቹ ጠቃሚ ወር ነው። በመሆኑም ጥቅም የሚሰጥ ጠቃሚት ወይም ጥቅምት ተብሎ የተጠራው በዚህ ምክንያት ነው።
ህዳር – ከመስከረም እና ከጥቅምት ወር በኋላ የሚመጣ ወር ነው። አንዳንዶች ህዳርን “ሃዳር” ከሚለው የግዕዝ ቃል ጋር በማዛመድ፤ “ከማደር” ጋር በማያያዝ – ታሪካዊ አመጣጡ ግዕዝ መሆኑን ለማስረዳት ብዙ ይጥራሉ። ሆኖም… የዚህ 3ኛ ወር ስያሜ የመጣው ባህር ተሻግሮ መሆኑ እውነት ነው። የህዳር ወርን… በግብጽ እና አረብ አገሮች፤ አቶር እና ሃቶር ሲሉት በእብራይጥ ደግሞ፤ አዳር በሚል ስያሜ ይታወቃል። በነገራቹህ ላይ ህዳር በግዕዝ ሲጻፍ ‘ኅ’ዳር ሲሆን፤ በትግርኛ ‘ሕዳር ነው። አማርኛው እንዳመቸው አድርጎ ሃሌታው ‘ሀ’ በመጠቀም ህዳር ይለዋል። የሆኖ ሆኖ የጥንት አባቶች የህዳር ወር ስያሜን ከጥንታዊው የባቢሎን ቋንቋ ወስደውታል። ይህ ካልሆነ ደግሞ በቸሃ ጉራጌ ህዳርን “ይዳር” ይለዋል። ስለዚህ ከውጭ ካላመጣነው ከራሳችን የጉራጌ ሴም ቋንቋ ተውሰነው ሊሆን ይችላል።
ታህሳስ – በግዕዝ ሐሰሰ ማለት፤ ተጓዘ ሄደ፤ ወይም አሰሰ እንደማለት ነው። የታህሳስ ወር ደግሞ ወታደሩም ነጋዴውም ከአገር ወዳገር የሚንቀሳቀስበት፤ የሚሄድበት፤ አገር የሚያስሥበት ወር ነው። ጉዞ ብሎ ተጓዘ እንደሚባለው… ሐሰሰ ብሎ ተሐሰሰ በመሆኑ፤ ተሃሰስ ወይም የጉዞ ወቅት ማለት በመሆኑ – ታህሳስ ቃሉን ያገኘው – ሀሰሰ ከሚለው ቃል መሆኑን መቀበል አይከብድም።
ጥር – በግዕዝ ጥሁር ማለት፤ ንጹህ ወይም ጥሩ ማለት ነው። የጥር ወር ሰብል ተሰብስቦ፤ ጥጋብ የሚመጣበት፤ ሰርግ እና ምላሽ፤ ድግስ እና ግብዣ የሚዘወተርበት ወር ነው። ለዚህም ነው – በግዕዝ ጥሁር፤ በአማርኛ ጥሩ ወይም ጥር የሚል ስያሜ ይዞ የቀረው። በሌላ በኩል ደግሞ – ለምሳሌ በጥንታዊው ደቡብ አረቢያ “ፀረረ” እና በጉራጊኛ – የጥር ወርን “ጥርር” በሚል ስያሜ ይጠሩታል። የዚህም መነሻ – በዚህ ወር ያለው ጠራራ ጸሃይ ሊሆን ይችላል። የጸሃይዋ መጥረር ወይም ማቃጠል አንደኛው ምክንያት ሊሆን ይችላል – “ጥር” የሚለውን ስያሜ ያስገኘልን።
የካቲት – በግዕዝ ከቲት ወይም ይከትት ማለት፤ መክተት ከሚለው የአማርኛ ቃል ጋር አቻ ናቸው። በገበሬው ዘንድ እህል ተሰብስቦ ወደ ጎተራ የሚከተትበት ወር ነው። በመሆኑም የመክተቻ ወር መሆኑን ለማመልከት – የካቲት ተባለ። ከቲት ማለት ከታች ማለት ሲሆን፤ የካቲት ደግሞ የመክተቻ ጊዜ እንደማለት ነው።
መጋቢት – የመጋቢት ወር ፍቺ ግልጽ ነው። በግዕዙም ቢሆን… ምግብ የሚመግበውን መጋቢ፤ አንስታይ ጾታ ወይም ሴት ከሆነች ደሞ መጋቢት ይለዋል። ጥቅምት ጠቃሚ ወር በመሆኑ፤ ጠቃሚቷ ወር ጥቅምት ተብላለች። አሁን ደግሞ ምግብ ሰጪ እና መጋቢ የሆነውን ወር – መጋቢት ያሉት ያለ ምክንያት አይደለም። በዚህ የበልግ ወር እህል እና ጥራጥሬ ብቻ ሳይሆን፤ ወፍ ዘራሽ እና የጫካ ፍራፍሬዎች ጭምር በየስፍራው ያድጋሉ። እንሰሳት እና አእዋፋትም እንደልባቸውና እንደሆዳቸው መጠን የሚመገቡበት ወር ስለሆነ፤ ይህን የምግብ እና የጥጋብ ወር መጋቢ ወይም መጋቢት ብለው ጠሩት።
ሚያዝያ – በአረብኛ – ማዛ ማለት መልካም ወይም ጥሩ መዓዛ ያለው ሽታ ማለት ነው። አንዳንድ ሰዎች ሚያዝያን ከመልካም ሽታ ጋር ያያይዙታል። እውነታው ግን ወዲህ ነው። ሚያዝያ የሚለው ቃል የሚወለደው፤ “መሐዘ” ከሚለው የግዕዝ ቃል ነው። መሐዘ ማለት፤ ጎለመሰ ወይም ሚስት ለመያዝ በቃ ማለት ነው። እንደልማድ ሆኖ ከግንቦት ወር ጀምሮ ሰርግ አይደረግም። ስለዚህ የጎለመሰ ወይም የመሐዘ ሰው፤ ሚዜ አደራጅቶ ሚስት የሚያገባው ከግንቦት ወር ቀድሞ በሚገኘው ወር ነው። በዚህ ምክንያት ወሩም… ትዳር መያዣ ወይም መሐዘ – መሐዘያ – መያዥያ ሲባል ቆይቶ፤ አማርኛው ሚያዝያ ብሎ ቃሉን ወረሰው።
ግንቦት – ትርጉም እና አመጣጡ አማርኛ ነው። በዚህ ወር መሰረት ተቆፍሮ ግንባታ የሚጀመርበት ነው። ለምሳሌ ፈለገ የሚለው ቃል ፍላጎት እንደሚባለው፤ ሰረቀ ብሎ ስርቆት እንደሚባለው፤ ገነባ ብሎ ግንቦት ይላል። በአገራችንም በዚህ ወር በርካታ የግንባታ ስራዎች ይከናወናሉ። የአባይ ግድብ ጭምር የተጀመረው በግንቦት ወር ነው።
ሰኔ – የቃሉ ምንጭ ትግረ ትግርኛ ነው። በትግረ ሰነየ ማለት መልካም ሆነ፤ ሰናይ ሆነ፤ አማረ ማለት ነው። ይህ ወር በአርጎብኛም ጭምር ሰነይ ይባላል። አማርኛው በሂደት ቃሉን… ከሰነይ ወደ ሰኔ ቀየረና የዚህ ወር መጠሪያ አድርጎታል።
ሐምሌ – በሐምሌ ወር ክረምት ይገባና ልምላሜ ይጀምራል።  የለመለመ ነገር ደግሞ ሐመልማል ይባላል። ሐመለ ማለት አበባ አፈራ ማለት አይደለም፤ አበበ ወይም ለመለመ ማለት ነው። ሐምለይ ማለት ደግሞ ለምለም ማለት ነው። በስነ ቃል ብዜት… ሐመለ፣ ሐምለይ እያለ ይበዛል። ደቡብ አርጎባም ቢሆን፤ እንዳማርኛ ወሩን ሐምሌ ነው የሚለው። የሆኖ ሆኖ… ሐምለይም በጊዜ ሂደት ወደአማርኛው አጠራር ሐምሌ ተባለ። በትግርኛ ሐምለ፤ ጉራጌ አገር ደግሞ ክስተን፣ ስልጢ፣ ወለኔ፣ ሙኸር ሐምሌን አምሌ ይሉታል።
ነሃሴ – የነሃሴ ወርን አመጣጥ ከአረብ አገር የሚያደርጉ አሉ። በእርግጥ ግብጽ እና አረቦች የጳጉሜን ወር “ናሴ” ብለው ይጠራሉ። ሆኖም 12ኛ ወር ማለትም ነሐሴን ከአረቦች ወሰድን የሚለውን አልስማማበትም። በግዕዝ ነሐሰ ማለት መስራት እና መገንባት ነው። በአገራችን በነሐሴ ወር የሚገነባ ነገር ብዙም ስለሌለ፤ ከግዕዙ መጣ ለማለት ያስቸግራል። የነሃሴ ትክክለኛ አመጣጥ ሊሆን የሚችለው፤ በዚህ ወር በሰማይ ላይ የምናያቸው ነሃሳማ ቀለማት ናቸው። እዚህ ላይ ስለነሃስ ለማያውቁ ሰዎች ጥቂት ማብራሪያ እንስጥ።
ነሃስ በኢትዮጵያውያን ዘንድ ለረዥም ጊዜ ይታወቃል። የቤተክርስቲያን ደቀል፣ መስቀል እና ጸናጽል ጭምር በነሃስ ይሰራል። ነሃስ ደግሞ በባህሪው እየቆየ ሲመጣ ቀለሙ ወደግራጫነት ይቀየራል። እጅግ ከበዙት የአለማችን ሃውልቶች መካከል የኒውዮርኳን Liberty of Statue መጥቀስ ይቻላል። በነጭነት እና በግራጫነት መካከል የሚገኝ ቀለም አላት። የነሃሴን ሰማይ ብንመለት፤ እንደአህያ ሆድ ነጭ፣ ግራጫ እና ጠቆር ብሎ እናየዋለን። እናም በኢትዮጵያ የነሃሴ ወር ሰማይ ነሃስ የመሰለ፤ ነሃሰይ የሆነ ነው። ነሃሰይ ማለት ደግሞ ነሃስማ ቀለም ማለት ሲሆን፤ አማርኛው ደግሞ ልክ ሰነይን ሰኔ፤ ሐምለይን ሐምሌ እንዳለው፤ ነሃሰይን ነሃሴ ብሎታል።
ጳጉሜ – እነዚህ 12 ወራት ወይም 360 ቀናት ካለቁ በኋላ፤ ሽርፍራፊና ቀሪ 5 ቀናት ይኖራሉ። እነዚህ ትርፍራፊ ቀናት በእንግሊዘኛው  epagomenal ኤፓጎሜናል ይባላሉ። በግሪክ ደግሞ ፓጉሜን ይሉታል፤ የግሪክ አቻ ትርጉም “የተረሱ ቀናት” ማለት ነው። ኢትዮጵያውያን ደግሞ… እነዚህ አምስት ቀናት ያሉበትን የቀናት ጥርቅም አንድ ላይ አድርገው፤ 13ኛ ወር አድርገውታል። ቃሉንም ከግሪክ በመዋስ፤ ፓጉሜን ጳጉሜ ብለነዋል።

 

Sunday, September 8, 2024

መሸቀጫ ሆንሽ!!! አብራሃም ለቤዛ


 



መሸቀጫ ሆንሽ!!! አብራሃም ለቤዛ

 

ሰንደቅ አላማ  የሚጥሉሽ የሚያነሱሽ፤ 

የጭንቅ ቀን  ያስታወሱሽ

ሲፈለጉ የሚረግጡሽ፤

የሚበጥሱሽ፤

ያ ያየነው በመስቀል በዓል፤

በአድዋ ክብር በዓል፤

ፖሊስ ከካድሬ ተናቦ ሰንደቅ ዓላማ ሲያረክስ፤

ከመኪና ሰንደቅ ጌጥ ሲልጥ ሲያሻው በመቀስ ሲመቅስ፤

ዛሬ ስልጣን የሚያጣ መስሎት ፤

በእምየ ኢትዮጵያ ተከልልሎ፤

ሰንደቅ ሰንደቅ ሰንደቅ ዓላማየ፤

እንዴት ተደረጎ ይደፈራል ይላል ፤

ሰንደቅ ይዘምራል፤

ሰንደቅ ይንከባከባል፤ ይሰቅል ያወረዳል፤

እባክህን እባክሽን አታዋክቡን፤

እንደለመድከው  እንደለመድሽው የካድሬነት ወጉን ፤

ለሰንደቅ ዓላማ ስትጠሩን ፤

ምናለ ብታስታዉሱ የረገጣችኋትን፤

ሰንደቅ ዓላማዋን የረገጣችኋትን የመቀሳችኋትን፤

ከወጣቱ አንገት ከሚሞተው ከሰንደቅ ዓላማ በፊት፤

ከከበዎሮ ከዕምነት ተቋም ከሚተጉት በፀሎት ፍታት፤

ከቀሚሷ መቅሳችሁ እናት ባገር እንዳንመስል፤

ያስደፋችሁ የእናት አንገት የአገር ክብር፤

ይረሳል ወይ ድርጊታችሁ ለራሳችሁ፤

ካድሬም ሾርት ሚሞሪ ነው ለካን፡፡

 


Sunday, July 28, 2024

ኢትዮጵያዊው ሠማዕት፡-አቡነ ጴጥሮስ ስሜነህ ደስታ (ዘመን መጽሔት ግንቦት 20 ቀን 2014 ዓ.ም )

 

 የ20ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ታላቅ ሠማዕት የሆኑት አቡነ ጴጥሮስ በ1875 ዓ.ም በቀድሞ አጠራር በሸዋ ጠቅላይ ግዛት በፍቼ ከተማ ተወለዱ። አቡነ ጴጥሮስ በሠማዕትነት እንደሚሞቱ መምህራቸው በትንቢት ነግሯቸውም ነበር። አለቃ ተጠምቀ የተባሉ ቅድስናን ከሊቅነት ጋር አስተባብረው የያዙ የቅኔ መምህራቸው አንድ ቀን አቡነ ጴጥሮስን ጠርተው ‹‹ሀይለማሪያም፣ አንተ ወደፊት ጳጳስ ትሆናለህ፤ በወቅቱም አረመኔ በዚች አገር ላይ ይሰለጥናል። ታዲያ አንተ ያኔ በነፍስህ ሳትሳቀቅ በሠማዕትነት እለፍ። ሠማዕትነት ክፍልህ ነው። አደራ!›› ብለዋቸውም እንደነበር ይነገራል።

ይኸውም ትንቢት ደርሶ አቡነ ጴጥሮስ በሠማዕትነት ለማለፍ በቅተዋል። አቡነ ጴጥሮስ የጵጵስና ስማቸውን ከማግኘታቸው በፊት መምህር ሀይለማሪያም ይባሉ ነበር። በልጅነታቸው ወላጆቻቸው ወደ ደብረሊባኖስ ገዳም በመውሰድ በሀይማኖትና በምግባር ተኮትኩተው እንዲያድጉ አድርገዋቸዋል። የቤተክርስቲያን ሥርዓተ ትምህርት ከንባብ እስከ ቅኔ ያሉትን ትምህርቶች በሚያስገርም ፍጥነት ከተማሩ በኋላ ወደ ቅኔው አውድማ ጎጃም በመሄድ በዋሸራ የቅኔ ትምህርታቸውን ፈፅመው መምህርም ሆነዋል። የዜማውንም ትምህርት ወደ ጎንደር በመሄድ

 ተምረዋል። በመቀጠልም ወሎ ቦሩ ሜዳ ላይ ወንበር ዘርግተው የመጽሐፍት ሚስጢር ይመግቡ ወደ ነበሩት ወደ ሊቁ አካለወልድ በመሄድ ዋና ዋናዎቹን የመጽሐፍት ትርጓሜ ማለትም ብሉያትን፣ ሐዲሳትን እና ሊቃውንትን በሚገባ አካሂደዋል።

ከዚህ በኋላ በ1900 ዓ.ም ወሎ አማራ ሳይንት ሄደው በምስካበ ቅዱሳን ገዳም ገብተው ወንበር ዘርግተው ለዘጠኝ ዓመታት ቅኔንና መጻሕፍትን አስተማሩ። በ1910 ዓ.ም ወደ ደብረሊባኖስ መጥተው ሥርዓተ ምንኩስናን ፈፀሙ። ከዚያም በመምህርነት ተሹመው ደብረ መንክራት ምሁር ኢየሱስ ገዳም ሄደው ለስድስት ዓመታት ካስተማሩ በኋላ በ1916 ዓ.ም እንደገና በዝዋይ ደብረጽዮን ቅድስተ ማሪያም ገዳም በመምህርነት ተሹመው ለሶስት ዓመታት አገልግለዋል። በ1919 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ በመምጣት የመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ መምህርና በቤተ መንግስት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የንስሀ አባትም ሆኑ።

ኢትዮጵያ በራሷ ተወላጅ ጳጳሳት ልጆች እንድትመራ ከ1600 ዓመታት በኋላ ስለተፈቀደላት በሀይማኖታቸውና በስነምግባራቸው የተመሰከረላቸው አምስት ደጋግ አባቶች ሲመረጡ አንዱ አቡነ ጴጥሮስ ነበሩ። በዚህ መሰረት ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የራሷን ጳጳስ ስትሾም አቡነ ጴጥሮስ ግንቦት 18 ቀን 1921 ዓ.ም ጵጵስና ተሾሙ። ከዚህ በኋላ አቡነ ጴጥሮስ ጳጳስ ዘምስራቀ ኢትዮጵያ ተብለው ተሹመዋል። ቤተክርስቲያንንና አገራችንን በፀሎታቸው፤ ሕዝብን በትምህርታቸው እየጠበቁ በተጋድሎ እየኖሩ ሳለ አረመኔው የኢጣሊያ ፋሺስት በ1928 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ላይ የግፍ ጦርነት አውጆ ሕዝቡንም በግፍ ይገድል ጀመር።

አቡነ ጴጥሮስ ይህንን ግፍ በማየታቸው ከአገራችን አርበኞች ጋር በመሆን በፀሎታቸው ሊዋጉት ተነሱ። ቀዳማዊ ኃይለሥላሴን ተከትለው ወደ ማይጨው ዘመቱ። ፋሺስቱ በማይጨው በመርዝ ጋዝ የተደገፈ ጦርነት ከማድረጉ የተነሳ የኢትዮጵያ ሠራዊት ቢበታተንም ከንጉሰ ነገስቱ ጋር ወደ አዲስ አበባ የተመለሱት አቡነ ጴጥሮስ ወደ ደብረሊባኖስ ሄደው ለሀገርና ለነፃነት መሞት ቅዱስ ተግባር መሆኑን ለሰላሌ አርበኞች በሚገባ አስተምረዋል። በደብረሊባኖስ ጫካዎች ውስጥ መሽጎ የነበረውን የእነ ደጅአዝማች አበራ ካሳ አርበኛ ጦር እና በሸንኮራ በኩል መሽጎ የነበረውን የእነ ፍቅረማሪያም አርበኛ ጦር እንዲሁም በምዕራብ ይመራ ከነበረው የእነ ደጃዝማች አባነብሶ ጦር ሶስቱም በአንድ ጊዜ ወደ መሃል አዲስ አበባ በመግባት አዲስ አበባ ላይ ሰፍሮ የነበረውን ፋሺስት ለመውጋት ታቅዶ የነበረውን እቅድ በመረጃ ክፍተት ምክንያት ውጤታማ ሳይሆን ቀረ።

መጀመሪያ የእነ ፍቅረማሪያም አርበኛ ጦር በኮተቤ አድርጎ የካ ሚካኤል ላይ ሲደርስ ተመትቶ ተመለሰ። ይሄኛው እንዳለቀ የእነ አባነብሶ ጦር በባቡር ጣቢያ መጣሁ ቢልም በጠላት ጦር ድጋሚ ተመትቶ ተመለሰ። መጨረሻ ላይ የእነ ደጃዝማች አበራ ካሳ አርበኛ ጦር በእንጦጦ በኩል ቢመጣም እሱም በጠላት ጦር ተመትቶ ተመለሰ። በዚህ አይነት ሁኔታ ሶስቱም የአርበኞች ጦር በመረጃ ክፍተት ምክንያት እየተመታ ወደ መጣበት ሲመለስ አቡነ ጴጥሮስ አብረው ከአርበኞች ጦር ጋር መመለሱን አልፈለጉትም። ይልቁንም ብችል ጠላት በኢትዮጵያ ላይ እያደረሰ ያለውን ግፍ በቅርብ እርቀት ሆኖ የሚመለከተውን ሕዝብ በማትጋት ጠላት ላይ እንዲነሳ አደርጋለሁ። ካልሆነም ደግሞ እዚሁ እሞታለሁ። በማለት ከአርበኞቹ ተነጥለው አዲስ አበባ ቀሩ።

ይሁን እንጂ ጠላት በመላው ከተማ ያሰማራቸው ባንዳዎች አቡነ ጴጥሮስን እንዳሰቡት ሊያንቀሳቅሷቸው አልቻሉም ነበር። በመሆኑም አቡነ ጴጥሮስ የሀገሬ ህዝብ ለጠላት እንዳይገዛ በአደባባይ አውግዤ ጠላትን ረግሜ በሠማዕትነት ባልፍ ይሻለኛል ብለው ራሳቸውን ለጠላት አሳልፈው ለመስጠት ወሰኑ። የፋሺስት ኢጣሊያ እንደራሴ ለነበረው ለራስ ኃይሉ ሄደው እጃቸውን ሰጡ። እሱም አቡነ ጴጥሮስን ወስዶ ለግራዚያኒ ሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም. አሳልፎ ሰጣቸው። ግራዚያኒም ግማሽ ቀን ባልሞላ ጊዜ ውስጥ እንዲገደሉ ወሰነባቸው።

አቡነ ጴጥሮስ በፈቃዳቸው እጃቸውን አሳልፈው ከሰጡበት ጊዜ ጀምሮ በጠላት የጥይት እሩምታ በሠማዕትነት እስካለፉበት ጊዜ ድረስ የነበረውን ሂደት ኮሪየሬ ዲላ ሴራ የተባለ ጋዜጣ ወኪልና የምስራቅ አፍሪካ ዜና መዋዕል አዘጋጅ የነበረው ፓጃሊ የተባለ ጋዜጠኛ እ.ኤ.አ ሰኔ 15 ቀን 1936 በአዲስ አበባ በነበረበት ጊዜ በአቡነ ጴጥሮስ ላይ የተሰጠውን ፍርድና የተፈፀመውን የግፍ ግድያ ባየውና በተመለከተው መንገድ እንደሚከተለው ጽፎት ነበር።

‹‹ሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም አቡነ ጴጥሮስ ተይዘው ወደ ግራዚያኒ ቀረቡ። በዚህም ጊዜ አቡነ ቄርሎስ የተባሉት ግብፃዊ ጳጳስ ቀርበው ለእስክድርያው መንበረ ፓትሪያርክ ምክር ቤት ሳታሰማ በአቡነ ጴጥሮስ ላይ አንዳች ነገር ማድረግ አይገባህም ሲሉ ለግራዚያኒ ነገሩት። አቡነ ቄርሎስ ይህን ማለታቸው በዲፕሎማቲክ ደረጃ ለዓለም ለማሰማትና የአቡነ ጴጥሮስ ህይወትን ለማትረፍ አስበው ነበር። ነገር ግን ግራዚያኒ የአቡነ ጴጥሮስን የሞት ፍርድ እንኳንስ እስከ ግብፅ ከአዲስ አበባ ውጪ ከመሰማቱ በፊት በግማሽ ቀን ውስጥ እንዲፈፀም መመሪያ አስተላለፈ።››

የምስራቅ አፍሪካ ዜና መዋዕል አዘጋጅ ፓጃሊ የአቡነ ጴጥሮስን መልካቸውንና ተክለ ቁመናቸውን ሲገልጽ ‹‹አቡነ ጴጥሮስ ቁመታቸው ረጅም፣ ፊታቸው ዘለግ ያለ፣ መልካቸውም ጠየም ያለ፣ አዋቂነታቸውና ትህትናቸው ከገፃቸው የሚነበብ ሲሆን በወቅቱ ለብሰውት የነበረው ልብስ የጵጵስና ጥቁር ካባ ያውም በጭቃ የቦካ ነበር።›› በማለት ይገልፀዋል።

በዚህ ሁኔታ ወደ ችሎት ቀረቡ። በችሎቱ የተሰየሙት ዳኞች ሶስት ሲሆኑ ጣሊያኖችና የጦር ሹማምንቶች ናቸው። የመሃል ዳኛው ኮሎኔል ነበር። የቀረበባቸው ወንጀል ሕዝብ ቀስቅሰዋል፣ ራስዎም አምፀዋል፣ ሌሎችም እንዲያምፁ አድርገዋል የሚል ነበር። ዳኛው ‹‹ካህናቱም ሆኑ የቤተክህነት ባለስልጣኖች፣ ሊቀጳጳሱ አቡነ ቄርሎስ የጣሊያንን መንግስት ገዢነት አሜን ብለው ሲቀበሉ እርስዎ ለምን አመፁ? ለምን ብቻዎን አፈንጋጭ ሆኑ? ›› ሲል ጠየቃቸው። አቡነ ጴጥሮስም በቆራጥነት ‹‹አቡነ ቄርሎስ ግብፃዊ ናቸው። ስለኢትዮጵያና ስለኢትዮጵያዊያን የሚገዳቸው ነገር የለም። እኔ ግን ኢትዮጵያዊ ነኝ። ኃላፊነትም ያለብኝ የቤተክርስቲያን አባት ነኝ። ስለዚህ ስለ አገሬና ስለ ቤተክርስቲያኔ እቆረቆራለሁ። ከዚህ በቀር ለእናንተ ችሎት የማቀርበው ነገር የለኝም። ለፈጣሪዬ ብቻ የምናገረውን እናገራለሁ። እኔን ለመግደል እንደወሰናችሁ አውቃለሁ። ስለዚህ በእኔ ላይ የፈለጋችሁትን አድርጉ። ግን ተከታዮቼን አትንኩ›› አሉ።

በጥይት ተደብድበው ሲገደሉ እንዲመለከት ተጋብዞ ለተሰበሰበው ሕዝብ ‹‹አረማዊ የሆነው የፋሺስት መንግሥት ቤተክርስቲያንን ለማቃጠል፣ ሕዝበ ክርስቲያንን ለመግደል፣ ሀይማኖትን ለማጥፋት፣ ታሪካችንን ለማበላሸት የመጣ ነው እንጂ በጎ ለመሥራት ስላልመጣ ለዚህ ለግፈኛ አትገዙ፤ ስለውድ አገራችሁ፣ ስለቀናች ሀይማኖታችሁ ተከላከሉ። ነፃነታችሁን ከማርከስ ሙታችሁ ስማችሁ ቢቀደስ ታላቅ ዋጋ ያለው ክብር ታገኛላችሁ። የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዚህ ለጠላት እንዳይገዛ አውግዣለሁ። የኢትዮጵያ መሬት ጠላትን ብትቀበል የተረገመች ትሁን። በፈጣሪዪ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተገዘተች ትሁን›› ብለው አወገዙ።

ቀጥለውም አቡነ ጴጥሮስ ችሎቱ ላይ እንዳሉ ሕዝቡ ሁሉ ስለሳቸው እያዘነ ሳለ መስቀላቸውን አውጥተው እየፀለዩ ሕዝቡን ባረኩት። ወዲያው የሞታቸው ፍርድ ሲሰማ ሕዝቡ በኢጣሊያ የእጅ ሰላምታ አይነት እጁን እንዲያነሳ ታዘዘ። በዚያን ጊዜ አቡነ ጴጥሮስ የሞታቸው ሰዓት መድረሱን አውቀው ሰዓታቸውን ከኪሳቸው አውጥተው ተመለከቱ። በወቅቱ ምንም ፍርሀት አይታይባቸውም ነበር። የሞታቸውን ፍርድ ያነብ የነበረ ኢጣሊያዊ ዳኛ ግን ይንቀጠቀጥ ነበር። ታላቅ ፍርሀትም በፊቱ ላይ ይታይ ነበር። የሞታቸው ፍርድ ከተነበበ በኋላ የፈረዱባቸውን ዳኞች ፀልይው በመስቀላቸው ባረኳቸው።

አቡነ ጴጥሮስ ሊገደሉ ሲወሰዱ ጥይት አልፎ ሌላ ሰው እንዳይመታ ግንብ ይፈለግ ጀመር፡ሩቅ ባለመሄድ ከመካነ ፍትሁ አስር ሜትር ግንብ ያለው መግደያ ቦታ ተገኘና ወደዚያው ተወሰዱ። ከገዳዮቻቸው አንዱ ‹‹ ፊትዎን መሸፈን ይፈልጋሉን ?›› ሲል ጠየቃቸው። ‹‹ይህ ያንተ ሥራ ነው›› ሲሉ መለሱለት። ወዲያው ቦታው እንደደረሱ ወንበር ቀረበላቸውና ፊታቸውን ወደ ግንቡ ጀርባቸውን ወደ ሕዝቡ አድርገው እንዲቀመጡ ተደረጉ። ከዚያም ስምንት ወታደሮች በስተጀርባቸው ሃያ እርምጃ ርቀው ተንበርክከው በተጠንቀቅ ቆሙ። ወዲያው አዛዡ ተኩስ በማለት ትእዛዝ ሲሰጥ ስምንቱም ተኩሰው መቷቸው። ነገር ግን በስምንት ጥይት ሳይሞቱ ቀሩ። መሞታቸውንና አለመሞታቸውን ለማረጋገጥ ዶክተር ተጠራ። ዶክተሩም እንዳልሞቱ አረጋገጠ። ከዚያ በኋላ አንድ ወታደር በሶስት የሽጉጥ ጥይት ራስ ቅላቸውን መትቶ ገደላቸው።

አቡነ ጴጥሮስ የተገደሉበት ቦታ መሀል አዲስ አበባ ዛሬ መታሰቢያ ሀውልታቸው ቆሞ በሚገኝበት ቦታ ላይ ነው በማለት የጋዜጣ ወኪልና የምስራቅ አፍሪካ ዜና መዋዕል አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ፓጃሊ ስለ አቡነ ጴጥሮስ ሠማዕትነት ምስክርነቱን ሰጥቷል። በተጨማሪም ደራሲና ጋዜጠኛ ጳውሎስ ኞኞ አቡነ ጴጥሮስ እንዴት ሞቱ ? ሲል በወቅቱ አቡነ ጴጥሮስ ሠማዕትነት ሲቀበሉ በቦታው በአካል በመገኘት ሁኔታውን ይከታተሉት የነበሩትን ሙሴ ፓይላክን ጠይቋቸው ሲመልሱ፣ ‹‹ አቡነ ጴጥሮስ የተገደሉ እለት እዚያው ነበርኩ። መጀመሪያ በእጃቸው ይዘው የነበረውን መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ተሳለሙት። ቀጥለው በያዙት መስቀል አማትበው ሕዝቡን ባረኩ። የኪሳቸውን ሰዓት አውጥተው ካዩ በኋላ መልሰው ከተቱት። ወዲያው ወታደሮች በእሩምታ ተኩስ ገደሏቸው። ይህ እንደሆነ አስገዳዩ ኮሎኔል ተመልካቹን ህዝብ አጨብጭቡ ብሎ አዘዘና ተጨበጨበ። ማታ ከአስገዳዩ ኮሎኔል ጋር ተገናኝተን ስንጫወት ‹በዚህ ቄስ መገደል እኮ ሕዝቡ ተደስቷል› አለኝ። ‹እንዴት? ›ብለው ‹አላየህም ሲያጨበጭብ !›አለኝ ‹ባታውቀው ነው እንጂ ሕዝቡ ሲናደድም ያጨበጭባል› አልኩት። እንዴት ቢለኝ እጄን አጨብጭቤ አሳየሁት። ከዚህ በኋላ የሆነው ቢሆን ትልቅ ማስታወሻ አግኝቻለሁ ብሎ አቡነ ጴጥሮስ ሲገደሉ ይዘውት የነበረውን መስቀል፣ መጽሐፍ ቅዱስ እና የኪሳቸውን ሰዓት አሳየኝ›› ብለዋል።

አቡነ ጴጥሮስ ሠማዕትነትን በተቀበሉበት ቦታ ላይ የመታሰቢያ ሀውልት ቆሞላቸዋል። የእኚህን ታላቅና ቅዱስ ሠማዕት አባት ክብርና ተጋድሎ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ከዘጠኝ ዓመት በፊት ቅዱስ ሰማዕት ብሎ በማፅደቅ በስማቸው በቅድስና ማዕረግ በስማቸው ታቦት ተቀርፆ ቤተክርስቲያን እንዲሠራላቸው ወስኗል። ይህም በተወለዱበት በሰሜን ሸዋ ስላሴ ሀገረስብከት በፍቼ ከተማ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተግባራዊ ሆኗል። ጉምቱ ባለቅኔ ፀጋዪ ገብረመድህን በግጥሙ ህያው አድርጓቸዋል። ይሁንና አፅማቸው የት እንደወደቀ ዛሬም ድረስ ሚስጢር እንደሆነ አለ። ደራሲ ፀሀይ መላኩ በአንድ ወቅት በኢቢኤስ ቴሌቭዥን ለብራና ልጆች ፕሮግራም በሰጠችው ቃለ ምልልስ የአቡነ ጴጥሮስ አስክሬን ፉሪ አካባቢ መኒሳ በምትባል ጉብታ ላይ ስለመቀበሩ የነገሯት አባት ስለመኖራቸው ተናግራለች።

በሰላሌ ዩኒቨርሲቲ የታሪክና ቅርስ አስተዳደር ትምህርት ክፍል ረዳት ፕሮፌሰር ስዩም መርጊያ አቡነ ጴጥሮስ ከህጻንነታቸው ጀምሮ ፆመኛና ፀሎተኛ እንደነበሩ እንዲሁም መንፈሳዊ ህይወት እንደሚታይባቸው፤ ዕድገታቸው በሀይማኖት ትምህርትና በመንፈሳዊ ህይወት የታጀበ እንደነበረ በመግለጽ ስለዕድገታቸው ያስረዳሉ። ከስጋዊው ይበልጥ መንፈሳዊው ህይወት ስለማረካቸው በፆም በጸሎት መወሰን ብቻ ሳይሆን፤ዓለም በቃኝ ብለው ምንኩስናን ተቀብለው በመምህርነት ከማገልገላቸው በተጨማሪ በወቅቱ አልጋ ወራሽ በነበሩት በራስ ተፈሪ ተመርጠው ቅዱስ ቄርሎስ መጽሐፍን ወደ አማርኛ እንዲተረጉሙ ከተመረጡ አምስት ሊቃውንት መካከል አንዱ ሆነው መሥራታቸውን ይገልጻሉ።

ረዳት ፕሮፌሰር ስዩም አቡነ ጴጥሮስ ለጣልያን አገዛዝ ባለመሸነፍ በአደባበይ ሕዝብ በተሰበሰበበት በጥይት ተደብድበው መሞታቸው በመንፈሳዊው ዓለም ሠማዕት እንደሚያደርጋቸው ጠቅሰው፤ በሠማዕትነታቸውም ፍቼ ከተማ ላይ በስማቸው የተሰየመ ካቴድራል መኖሩን እና በቅጥር ግቢው ውስጥ አዲስ አበባ ከተማ ያለውን የሚመስል ሀውልት በመታሰቢያነት የቆመላቸው መሆኑን ይናገራሉ። በፍቼ ከተማ ላይ በከተማ አስተዳደሩ በሰላሌ ኦሮሞ ማዕከል ውስጥ በስማቸው የተሰየመ የመሰብሰቢያ አዳራሽ እንዳለም ይገልጻሉ።

የአቡነ ጴጥሮስ ተጋድሎ ከጥቅምና ከማዕረግ በላይ ኢትዮጵያን ማስቀደም እንደሚገባ እና አገርን ከጠላት ለመከላከል ሀይማኖትም ሆነ ብሔርን ወይም ሌላ ነገርን ማዕከል አድርጎ መነሳት እንደማያስፈልግ የሚያሳይ ነው በማለት ረዳት ፕሮፌሰር ስዩም ያስረዳሉ።

በጅማ ዩኒቨርሲቲ በታሪክ ትምህርት ክፍል በተባባሪ ፕሮፌሰርነት መምህርና ተመራማሪ የሆኑት ዶክተር ፀጋዬ ዘለቀ የአቡነ ጴጥሮስ የሠማዕትነት ተግባር በወቅቱ ለነበሩ ኢትዮጵያውያን፣ ለኢትዮጵያ መሞት ክብር እንደሆነ በማሳያነት የሚጠቅሱት መሆኑን እና የአርበኝነት ትግሉ እንዲፋፋም ከፍተኛ መነቃቃት የፈጠረ እንደሆነ ይጠቅሳሉ። በወቅቱ ለነበሩት ብቻ ሳይሆን የአሁኑም ሆነ የቀጣዩ ትውልድ የእሳቸውን ተግባር በማየት አገርን መውደድና ለአገር መቆም ምን እንደሚመስል ሊማርበት የሚያስችለው ነው ይላሉ።

ስሜነህ ደስታ

ዘመን መጽሔት ግንቦት 20 ቀን 2014 ዓ.ም  


Friday, January 12, 2024

A reform culminated in changing logos

Abiy Administration in the name of reform, he is aggressively engaged in changing organization logos and in some case seems elimination of long held and accustomed logos that bear the lion.  A reform culminated in changing logos Abiy who claimed a master of all, call his log changing reform ergonometric that bring mood of employees hardworking and then he dragged the nation in to defaulted. An extravagant expenditure on non-strategic areas such as lavish palace to bring his mood of primer tenure.The argument by some institutions like federal police doesn't hold water

Ethiopian Federal Police - Posts | Facebook